
ለአፍሪካ ዋንጫ ለሴካፋ ዞን የታዳጊዎች የማጣርያ ውድድር ብሔራዊ ቡድኑን የሚወክሉትን ተጨዋቾች ለመመልመል ሥራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ገለጸ ።

ፌዴሬሽኑ እንዳለው በቀጣይ ዓመት መጀመርያ ለሚካሄዱት ከ17 እና ከ20 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ሴካፋ ዞን የማጣርያ ውድድሮች ለሁለቱም የዕድሜ እርከን ብሔራዊ ቡድኖቻችን ብቁ የሚሆኑ ተጫዋቾችን ለመለየት እንዲያስችል የናሽናል ካምፒንግ የመጀመርያ ምዕራፍ ዛሬ ተጀምሯል ብሏል።

በሁለቱ የዕድሜ እርከኖች በጠቅላላው 81 ተጫዋቾች ትናንት ሐምሌ 18 የተሰባሰቡ ሲሆን የናሽናል ካምፒንጉ የመጀመርያ ምዕራፍ እስከ ዓርብ ሐምሌ 24 ድረስ የሚቆይ ይሆናል ሲልም ገልጿል።

በመስከረም ወር ታንዛንያ ላይ እንደሚካሄድ በሚጠበቀው ከ20 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣርያ ውድድር ላይ ለሚሳተፈው የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ብቁ የሚሆኑ ተጫዋችን ለመመልመል በዚህ ምዕራፍ 41 ተጫዋቾችን በማሰባሰብ የምልመላ ሒደት የተጀመረ ሲሆን በናሽናል ካምፒንጉ ላይ ከ2 ወራት በፊት በሞሮኮ በተካሄደው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ድንቅ ጉዞ አድርጎ ከነበረው ቡድን፣ በአፍሪካው ዋንጫ ስብስብ ውስጥ መካተት ያልቻሉ እና በባለፈው ዓመት ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ካምፒንግ ተከታታይ ስልጠና ሲያገኙ የነበሩ እንዲሁም ከኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ፕሪምየር ሊግ ውድድር ላይ የተመለመሉ ተጫዋቾች መካተታቸውን ገልጿል።
ከዚህ ሌላ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን የማጣርያ ውድድር በሩዋንዳ አስተናጋጅነት ጥቅምት ወር ላይ እንደሚካሄድ ሲጠበቅ በዚህ ውድድር ላይ ተሳታፊ ለሚሆነው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ቡድን ተጫዋቾችን የመመልመል ሒደት ለማከናወን 40 ተጫዋችችን በማሰባሰብ የናሽናል ካምፒንጉ ተጀምሯል። ከሁለት ሳምንት በፊት በአዲስ አበባ እና አዳማ ከተማ የውስጥ ውድድሮች ላይ ተመልምለው የሪጅናል ካምፒንግ በማከናወን ስልጠና የተሰጣቸው 40 ታዳጊዎች የዚህ ካምፒንግ አካል ሆነዋል በማለትም ተናግሯል።
የናሽናል ካምፒንግ የመጀመርያ ምዕራፍ ዛሬ ሲጀመር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ ሜዳ በሁለቱም የዕድሜ እርከን የተመረጡት ሁሉም ተጫዋቾች የአካል ብቃት ምዘና ተከናውነው በማስከተል ቡድኖቹ በተናጠል የእርስ በርስ ጨዋታ በማከናወን የተጫዋቾች ብቃት ምዘና መካሄዱን ፌዴሬሽኑ አሳውቋል።
