
(ከምስጋናው ታደሰ ጋር ያደረገው ቆይታ)
ከአሰልጣኝ ሳምሶን አየለ ጋር በስምምነት የተለያየው ኢትዮጵያ ቡና አንጋፋውን አሰልጣኝ ገ/መድህን ሀይሌን በሁለት ዓመት ውል በዛሬው ዕለት አስፈርሞታል።
በተጨዋችነት ዘመኑ በቅ/ጊዮርጊስና በኢትዮጵያ ብ/ቡድን ስመ ገናና የነበረው ገ/መድህን በአሰልጣኝነት ዘመኑም በርካታ ክለቦችን አሰልጥኖ ስኬታማነቱን ማስመስከር ችሏል። ከሶስት የተለያዩ ክለቦች (ከጅማ አባጅፋር፣ መቀሌ 70 እንደርታ እና ከኢትዮጵያ መድህን) ጋር የፕሪሚየር ሉጉን ዋንጫ ያነሳ ብቸኛው አሰልጣኝ ነው።

አሰልጣኝ ገ/መድን ለቡና ዛሬ ማምሻውን ፊርማውን በይፋ ካኖረ በኋላ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ተከታዩን ቆይታ አድርገን ነበር።
ጥያቄ፦ እንደምን አመሸህ ገሬ?
ገ/መድን፦ እግዚአብሔር ይመስገን! እንዴት አመሸህ ምስጌ?
ጥያቄ፦ ስምህ ከተለያዩ ክለቦች ጋር ተያይዞ ሲነሳ የነበረ ቢሆንም በስተመጨረሻ ግን ወደ ኢትዮጵያ ቡና አምርተሃል…
ገ/መድን፦ ልክ ነህ የሚፈልጉኝ ክለቦች የነበሩ ቢሆንም ምርጫዬ ግን ቡና ሆኗል። በነገራችን ላይ ዜናው ቀን ላይ በማህበራዊ የትስስር ገፆች ሲወጣ ገና ፊርማዬን አላኖርኩም ነበር። የወረቀት ጉዳዮች አልቀው በይፋ ፊርማዬን ያኖርኩት ቅድም አንተ የደወልክልኝ ሰዓት አመሻሹ ላይ ነበር። እዛ ፕሮግራም ላይ ስለነበርኩ ነው ስልክህን ያላነሳሁልህ፤ ለዛ ነው ስጨርስ መልሼ የደወልኩልህ…
ጥያቄ፦ ከቡና በፊት እኮ ስምህ በስፋት ሲነሳ የነበረው ከፋሲል ከነማ ጋር ነበር…
ገ/መድን፦ ልክ ነህ…ፋሲሎች አናግረውኝ ነበር። ሁሉም እንደሚያውቀው ፋሲል ለብ/ቡድን ጭምር ተጨዋቾችን የሚያስመርጥ ትልቅ ክለብ ነው። በዛ ክለብ ውስጥ መስራት የማይፈልግ አሰልጣኝ አለ ብዬ አላስብም፤ እኔ ግን ኢትዮጵያ ቡናን ልመርጥ ችያለሁ።
ጥያቄ፦ እኔ እንደውም የሰማሁት ፋሲሎች 15 ሚሊዮን ብር የፊርማ ክፍያ አቅርበውልህ እንደነበር ነው…ቡናን የመረጥከው ታዲያ ከዚህ የተሻለ ገንዘብ አቅርቦልህ ነው ማለት ነው?
ጥያቄ፦ ኖኖኖ…እንደዛ አይደለም። ምስጌ እኔና አንተ ረጅም ዓመታት የምንተዋወቅ ሰዎች ነን። ዕውነቱን ነው የምነግርህ፤ ፋሲሎች አናግረውኛል። በጣም ጥሩ ሰዎች ናቸው። በዚህ አጋጣሚ አክብረውኝ ስለመጡ ላመሰግናቸው እወዳለሁ። ብዙ ብንነጋገርም 15 ሚሊዮን ብር የፊርማ ክፍያ የተባለው ግን ትክክል አይደለም። በሌሎች ጉዳዮች ላይ ተነጋገርን እንጂ የገንዘቡ ጉዳይ ላይ ገና አልደረስንም ነበር። ቡናም ከዚህ በላይ አልሰጠኝም።

ወደ ዕውነታው ስንመጣ ቡናዎች ያናገሩኝ ከፋሲል አስቀድመው ነው። እኔም ውድድሩ ሲያልቅ ቅድሚያ የምደራደረው ከእነሱ ጋር እንደሆነ ቃል ገብቼላቸው ነበር። ስለዚህ ያንን ቃሌን መጠበቅ ነበረብኝ። ፋሲሎች ያናገሩኝ ለቡና አመራሮች ቃል ከገባሁላቸው በኋላ ነው። ያ ካልተሳካ ግን በቀጣይነት ከእነሱ ጋር የጀመርኩት ድርድር ሊቀጥል ይችል ነበር። የነገርኳቸውም ይሄንኑ ነው።
ጥያቄ፦ እሺ ኢትዮጵያ ቡና ምን ያህል የፊርማ ክፍያ ከፈለህ?
ገ/መድን፦ (ከት ብሎ ስቆ) አንተ ኢትዮ ኤፍ.ኤም 107.8 ምን ያህል ይከፍልሃል?
ጥያቄ፦ ምን ያደርግልሃል?
ገ/መድን፦ (አሁንም እየሳቀ) የእኔስ ታዲያ ምን ያደርግልሃል?… ወደ ቁምነገሩ ስንመጣ ግን መቼስ በነፃ ነው የምሰራው አልልህም… የሚገባኝን ሊከፍሉኝ ተስማምተን ነው የፈረምኩት። ከሁሉም በላይ ግን አስፈላጊው ነገር ክለቡን ወደ ሻምፒዮናነት መመለሱ ላይ ነው። ሁለታችንም ወገኖች ትኩረት ሰጥተን ለረጅም ጊዜያት ስንነጋገር የነበረው በዚህ ጉዳይ ላይ ነው። ውጤቱ እስከመጣ ድረስ እኮ ገንዘቡም አብሮ ይመጣል። ቅድሚያ የሰጠነውም ውጤቱ ላይ ነው…
ጥያቄ፦ ብዙ አሰልጣኞች “ቡናን ማሰልጠን ከደጋፊው ብዛት አንፃር ጫናው ከባድ ነው” ይላሉ፤ ትስማማለህ?
ገ/መድህን፦ ዕውነት ለመናገር የአሰልጣኝነት ህይወት በጣም ከባድ ነው። የትኛውንም ክለብ ብትይዝ ጫናው ከባድ ነው። እንደ ቡና ዓይነት የበርካታ ደጋፊዎች ባለቤት የሆነ ክለብ ስትይዝ ደግሞ ዕውነት ነው ጫናና ግፊቱ ከዚህም የባሰ ነው። ነገር ግን እኔ በባህሪዬ ጫና የመሸከም አቅም አለኝ ብዬ አስባለሁ። ጅማ አባ ቡና እና መቀሌም እኮ በርካታ ደጋፊዎች አሏቸው። ያንን ተቋቁሜ ነው የሊጉን ዋንጫ ያነሳሁት። ስለዚህ በዚህ ዙሪያ ብዙም ስጋት የለብኝም።
ሌላው ለመግለፅ የምፈልገው ነገር በክለብ ደረጃ ለቅ/ጊዮርጊስ ልጫወት እንጂ በአሰልጣኝነት ዘመኔ እኮ ቡናን አሰልጥኛለሁ። አሁን ለሁለተኛ ጊዜ ነው የመጣሁት። ደጋፊውን በደንብ አውቀዋለሁ። ለክለቡ ህይወቱን የሚሰጥ ምርጥ ደጋፊ ነው። ለክለቡ ይዘምራል፤ በተቃራኒው ደግሞ በተጋጣሚው ላይ ተፅዕኖ ለመፍጠር የተቻለውን ሁሉ ጫና ይፈጥራል። ይሄ በየትኛውም ክለብ ውስጥ ያለ ነው። የቡና ደጋፊ በአሰልጣኞች ቡድን አባላትም ላይ ሆነ በክለቡ አመራሮች ላይ ተቃውሞውን የሚያሰማው እኮ ከውጤት መናፈቅ አንፃር እንጂ የግል ጥላቻ ኖሮት አይደለም። ይሄ ደግሞ ማንቸስተር ዩናይትድ እና ሪያል ማድሪድን በመሳሰሉ የዓለማችን ታላላቅ ክለቦች ሁሉ የሚያጋጥም ነው። የቡና ደጋፊ እኮ ከሜዳ ውጪ ሰላማዊ ነው…
ጥያቄ፦ በዚህ አጋጣሚ ደጋፊውን ምን ትለዋለህ?
ገ/መድን፦ ያው ለእነሱ ትልቅ አክብሮት እንዳለኝ ልነግራቸው ነው የምፈልገው። ቡናን ወደ ሻምፒዮናነት ለመመለስ የእኔና የባልደረቦቼ ጥረት ብቻ ሳይሆን የእነሱ ድጋፍም ያስፈልገናል። አንዳንዴ ነገሮች ጥሩ ባይሆኑ እንኳን በሰከነ ሁኔታ እየተመካከርን እንድንጓዝ ነው የማስበው።
ጥያቄ፦ አሁን ቡናን በይፋ ተረክበሃል…ክለቡን የሚለቁና የሚመጡ ተጨዋቾች አሉ?
ገ/መድን፦ ይሄ ግድ ነው። ሊጉ ላይ እንደመቆየቴ መጠን የራሴን ክለብ (መድህንን) ብቻ ሳይሆን የሌሎች ክለቦችን ክፍተቶችም ስገመግም ነበር። ቡና ውስጥ ኮንትራታቸውን የጨረሱ እና የውጪ ሙከራ ላይ ያሉ ልጆች አሉ። ኮንትራት ከጨረሱት ውስጥ የምፈልጋቸው ሊኖሩ ይችላሉ። ለመቀጠል ፈቃደኛ ከሆኑ የተወሰኑት ሊቀጥሉ ይችላሉ። ከዛ በተረፈ ከቦርዱ ጋር መነጋገር ከጀመርኩበት ጊዜ አንስቶ ክለቡ ክፍተቶች ባሉበት ቦታዎች ላይ ቢመጡ ሊያግዙን ይችላሉ ብዬ ያሰብኳቸውን ተጨዋቾች ለማስፈረምና ጠንካራ ቡድን ለመስራት እሞክራለሁ።
ጥያቄ፦ ክለቡን በዛሬው ዕለት በይፋ ስትረከብ ዋንኛ ግብህ ምን ሆኖ ነው ሀላፊነቱ የተሰጠህ?
ገ/መድን፦ ከቦርዱ ጋር ብዙ አውርተናል። የሁለት ዓመት ኮንትራት ነው የተፈራረምኩት። ለራሴ ማጋነን ሳይሆን በጫና ውስጥ መስራት የምችል ሰው ነኝ። ሁሉም እንደሚያውቀው ከዚህ ቀደም ከሶስት ክለቦች (ከጅማ፣ መቀሌ እና መድን) ጋር የሊጉን ዋንጫ አንስቻለሁ። አሁን ደግሞ ወደ ቡና የመጣሁት አራተኛው የሊጉ ሻምፒዮን ክለቤ ላደርገው ነው። ከተሳካልን በመጀመሪያው ዓመት…ካልሆነልን ደግሞ በሁለተኛው ዓመት። በዚህ ጉዳይ ከቦርድ አባላቱ ጋር በሰፊው ከተነጋገርን በኋላ ነው ተስማምተን የፈረምኩት። በዚህ አጋጣሚ ደጋፊውም ከጎናችን እንዲሆን ጥርዬን አቀርባለሁ።
ጥያቄ፦ በጣም አመሰግናለሁ ገሬ!!
ገ/መድን፦ በስማበለው ከሚናፈሱት ወሬዎች ውጪ ቀጥታ ከእኔ አንደበት ለመስማት ላደረግከው ሙከራ እኔም በጣም አመሰግናለሁ !
