
በፊፋ ግሎባል የእግር ኳስ ልማት ዳይሬክተር አርሰን ቬንገር የተዘጋጀው የፊፋ ተሰጥኦ ልማት እቅድ Talent Development Scheme (TDS) በአባል ሀገራት ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣት የእግር ኳስ ተጫዋቾች በተዋቀሩ እና ዘላቂ የልማት መንገዶች እንዲለዩ፣ እንዲያዳብሩ እና እንዲያሳድጉ ለመርዳት የተነደፈ እቅድ ነው። ይህን መሠረት አድርጎ የሚመራ አሰልጣኝ አስፈላጊ በመሆኑ ይህንን እቅድ ለማስፈፀም በዛሬው ዕለት የኢ/እ/ፌ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ባሕሩ ጥላሁን ከፊፋ ታለንት አሰልጣኝ ሳይፕሪያን አሹ ጋር የቅጥር ውል ተፈራርመዋል።
በመርሐ ግብሩ አቶ ባሕሩ በርካታ ሀገራት በእዚህ ስልጠና ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆኑ እንደሚፈለግና ዋነኛ አላማው የሀገራትን የእግር ኳስ ልዩነት ማጥበብ እንደሆነ ይህንን ማድረግ ደግሞ የሚቻለው እግር ኳሱ ዘመን በደረሰበት እና ዓለም በሚፈልገው መልኩ መመራት ሲችል መሆኑን ገልጸዋል።

አቶ ባሕሩ አክለውም የኢ/እ/ፌ ለፊፋ ይህንን ጥያቄ በተደጋጋሚ እንዳቀረበ እና በጥያቄው መሰረት መሟላት የሚገባቸውን መስፈርቶች እንዲያሟላ በታዘዘው መሠረት በሟማላቱ አሠልጣኝ ሳይፕሪያን አሹ
መመደባቸውን ገልፀዋል።
ፊፋ ለፕሮግራሙ በጀት በመመደብ የአሰልጣኝ ቅጥር መስፈርቶችን በማውጣት አወዳድሮ ቅጥሩን በማካሄድ በየሀገራቱ ይመድባል። ይህንን ተከትሎ ከ2019 እስከ 2021 የደቡብ ሱዳን ዋና አሰልጣኝ ሆነው ያገለገሉት እንዲሁም በዕድሜ እርከን የካሜሩንን ከ20 ዓመት በታች እና ጅቡቲ ከ20 ዓመት በታችን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ እና የክለብ ቡድኖችን የመሩት እንዲሁም ለሌይስተር ሲቲ ከ21 ዓመት በታች ረዳት አሰልጣኝ በመሆን ያሰለጠኑት በተጨማሪም በተጫዋችነት ዘመናቸው በካሜሩን ውስጥ ለሚገኙ በርካታ ክለቦች እና በጀርመን ከፎርቱና ዱሰልዶርፍ 2 እና ከቦሩሲያ ሞንቼንግላድባች ጋር ተጫውተው ያሳለፋ አንጋፋ አሰልጣኝ የሆኑት ጀርመናዊው ሳይፕሪያን አሹ ለኢትዮጵያ መመደብ ችለዋል።
ለሁለት ዓመታት በኢትዮጵያ እንዲያሰለጥኑ የተሾሙት የተሰጥኦ አሰልጣኙ ሳይፕሪያን አሹ የተሰጥኦ ልየታ፣ የተጫዋቾችን ልማት፣ የአሰልጣኞችን ትምህርት እና ለወጣት ተጫዋቾች ውጤታማ የልማት መንገዶችን ለማቋቋም ከፌዴሬሽኑ የቴክኒክ ቡድን ጋር በቅርበት ይሰራሉ።
ይህ ቅጥር ተሰጥኦ ያላቸው ወጣት የእግር ኳስ ተጫዋቾች ጥራት ያለው ስልጠና እና የልማት እድሎችን እንዲያገኙ ለማረጋገጥ የተጀመረውን መንገድ ለማጠናከር የሚረዳ ነው።
በኢትዮጵያ የሚካሄደው ስልጠና ከመላው ሀገሪቷ የሚውጣጡ እድሜቸው ከ15 ዓመት በታች ለሆኑ 40 ታዳጊዎች ሲሆን ሴት ታዳጊዎችም ተሳታፊ ይሆናሉ።
በልየታው የተመረጡት ሰልጣኞች ለቀጣይ ሁለት ዓመታት በካፍ የልህቀት ማዕከል መኖሪያቸውን በማድረግ መደበኛ ትምህርታቸውን እየተማሩ ጎን ለጎን በፊፋ በተቀረፀ ማንዋል መሠረት በተሰጥኦ አሰልጣኝ ሳይፕሪያን አሹ አማካኝነት የማበልፀግ ሥራ ይሰራል።
የልየታ ስራውን ለመሥራት በቅርቡ በሚጀመረው የሊግ ሂደት ጋር በተቆራኘ መልኩ በከተሞች ላይ የሚገኙ የተሰጥኦ ልየታ ባለሙያዎች ተከታታይ ስልጠና በመስጠት እና ቁጥራቸውን በማብዛት የልየታ ስራው በእነሱ አማካኝነት የሚሰራ ይሆናል።
በ Talent Development Scheme (TDS) ፕሮጀክት እስከ አሁን 18 የአፍሪካ ሀገራት አካዳሚዎች ስራ የጀመሩ ሲሆን ኢትዮጵያ 19ኛዋ ሀገር ሆናለች ።
