
🔷 ቅድመ ታሪክ፦
ከአራት ወራት በፊት የአውሮፓ እግርኳስ ማህበር በፍሬንዲሽፕ ካፕ ብትሳተፉልን ብሎ ለኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ግብዣ ላከ፤ ፌዴሬሽኑም ጥሪውን ተቀበለ፤ የኢትዮጵያ ከ18 አመት በታች ሴቶች ብሄራዊ ቡድን 30 ልዑካንን ይዞ ወደ አዘጋጇ ሃገር ቱርኪዬ ሄደ፤ ቡድኑ ከኡራጋይ፣ ኮስታሪካና ኖርዌይ ጋር ተደለደለ፤ በመጀመሪያ ጨዋታው ኡራጋይን 3-0 አሸነፈ፤ በሁለተኛው ኮስታሪካን 1-0 ረታ፤ በሶስተኛው የምድብ ጨዋታ በኖርዌይ 1-0 ተሸነፈ፤ በመጨረሻም በአዘጋጇ ቱርኪዬ 3-1 ተሸንፎ ከስምንት ሃገራት አራተኛ ሆኖ አጠናቀቀ
🔷 የውዝግቡ መነሻ፦
ከመጋቢት 29 እስከ ሚያዚያ 9/2018 በፍሬንዲሽፕ ካፕ የተሳተፈው የኢትዮጵያ ከ18 አመት በታች ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ውድድሩን እንዳጠናቀቀ ፌዴሬሽኑ ለ30 የቡድኑ አባላት ለእያንዳንዳቸው 100 ዶላር አበረከተ፤ ይህ ውሳኔ ግን ተጫዋቾቹን አስከፋ፤ የኢትዮጵያ ተጫዋቾች ለብሄራዊ ቡድን ግዴታ ከሃገር ሲወጡ በቀን 50 ዶላር አበል ይሰጣቸዋል፤ ከአስር ቀን በላይ ቱርኪዬ የቆዩት ተጓዦችም ቢያንስ እያንዳንዳቸው 500 ዶላር ጠብቀው ነበር፤ 100 ዶላር ብቻ ሲሰጣቸው ግን አንቀበልም አሉ፤ ሁሉም 22 ተጫዋቾች ገንዘቡን አልወሰዱም፤ ቅሬታቸውን ያደረሱን ተጫዋቾች እንደሚሉት እለታዊ አበል እንደሌለ ቀድሞ ስላልተነገረንና የሰጡን ትንሽ ስለሆነ ሁላችንም በጋራ አንቀበልም ብለናል፤ የቡድኑ አሰልጣኞችና ሌሎች የቡድኑ አባላት ግን የፌዴሬሽኑን 100 ዶላር ተቀብለዋል ይላሉ
🔷 የፌዴሬሽኑ ምላሽ፦
የተጫዋቾቹን ቅሬታ መነሻ በማድረግ አቶ ባህሩ ጥላሁን የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ማብራሪያ እንዲሰጠን ጠየቅን፤ ምላሹም ተከታዩ ነው፦
“የቱርኪዬ ጉዞ በእኛ አመታዊ የውድድር መርሃ ግብር ውስጥ አልነበረም፤ የሴቶች ከ18 አመት በታች ብሄራዊ ቡድን የሚባልም የለንም ፤ የአውሮፓ እግርኳስ ማህበር ጥሪ ሲያቀርብልን ጊዜው አጭር ቢሆንም ቡድን አዋቅረን ላክን፤ ተጫዋቾቹ የውጭ ክለቦች ምልመላ አይን ውስጥ እንዲገቡ ብሎም ከሀያ አመት በታች ብሄራዊ ቡድን ላለበት ጨዋታ በእድሜ ቅርብ የሆኑት ልምድ እንዲወስዱ በሚል አላማ ነው የተሳተፍነው፤ ከመሄዳቸው በፊት ለውድድሩ በጀት እንደሌለን፣ ሃገር ቤት ሲዘጋጁ የኪስ ገንዘብ እንደምንሰጣቸው፣ ከሃገር ሲወጡ ግን እለታዊ አበል እንደሌላቸው ሆኖም ለሁሉም የቡድኑ አባል ለእያንዳንዱ የኪስ ገንዘብ 100 ዶላር ብቻ እንደምንሰጥ በወቅቱ በቡድን መሪውና በቴክኒክ ዳይሬክተሩ በኩል ነግረናቸዋል፤ ይህንን ተከትሎ ኮቺንግ ስታፉና ከፌዴሬሽኑ ተወክለው የሄዱት ብሩን ተቀብለዋል፤ ተጫዋቾቹ ግን ይህ ገንዘብ ያንሰናል አንቀበልም የሚል ምላሽ ነው የሰጡን፤ በመሆኑም ፌዴሬሽኑ ያዘጋጀላቸውን ገንዘብ ሳይቀበሉ ቀርተዋል፤ በነገራችን ላይ የትራንስፖርት፣ የሆቴልና ሌሎች ወጪዎችን የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ነው የሸፈነልን፤ እኛ ያወጣነው ለቪዛ ክፍያ ብቻ ነበር፤ እሱንም ማህበሩ ሰሞኑን መልሶልናል፤ ከዛ ውጪ ለአበል ተብሎ ተጨማሪ ገንዘብ አልተሰጠንም፤ ፌዴሬሽኑ ከራሱ ካዝና ነው የ100 ዶላሩን የኪስ ገንዘብ ያዘጋጀው” ብሎናል ዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ ባህሩ
🔷 የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ማረጋገጫ፦
ጉዳዩን ይበልጥ ለማጥራት የውድድሩ ዋና አዘጋጅ ለሆነው የአውሮፓ እግርኳስ ማህበር በሚዲያ ክፍሉ በኩል በኢሜል ጥያቄ ልከን ነበር፥ ተከታዩን መልሰውልናል
“ሁሉም ተሳታፊ ቡድኖች በቱርኪዬ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዋና ፅህፈት ቤት አጠገብ በሚገኘው ሆቴል ነበር ያረፉት፤ የሆቴልና የትራንስፖርት አቅርቦት ወጪዎችን በሙሉ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ነው የሸፈነው፤ የትኛውም ተሳታፊ ቡድን ግን የቀን ውሎ አበል ከማህበሩ አላገኘም፤ ሆኖም የፋይናንስና ሌሎች ድጋፎች ለቡድኖቹ ቀርበዋል” የሚል ምላሽ ሰጥተውናል (የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር በኢሜል የመለሰልን ማብራሪያ በመጀመሪያው ሃሳብ መስጫ ላይ ይገኛል)
🔷 የ100 ዶላሩ መጨረሻ፦
ተጫዋቾቹ ገንዘቡ አንሶናል፥ መጠኑም ይህ ብቻ መሆኑ ስላልተነገረን ዶላሩን አንወስድም ብለው እስካሁን በውሳኔያቸው ፀንተዋል፤ ፌዴሬሽኑ ደግሞ ቀድመን አሳውቀናቸዋል፥ ተጫዋቾቹ ብቻ ናቸው አንወስድም ያሉት እንጂ ሌሎቹ ልዑካን ተቀብለዋል ይላል፤ የተጫዋቾቹ ዶላር መጨረሻ ታድያ ምን ሆነ ብለን የፌዴሬሽኑን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ባህሩን ጠይቀነው ነበር፤ መልሱ፦ “አንቀበልም ስላሉ ወደ ፌዴሬሽኑ አካውንት ተመልሷል”
(ታምሩ ዓለሙ)
